Sunday, January 6, 2013

ሚሚ ስብሐቱ እና የሙታን ዲሞክራሲ



ዳኛቸው አሰፋ(/)
January 05, 2013                                                                                             
አዲስ አበባ

 የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ሚሚ ስብሐቱና ጓደኞቿየጋዜጠኞች ክብ ጠረጴዛበተሰኘ ፕሮግራም እኔ ላይ ለሰነዘሩት ስድብ በዋናነት መልስ ለመስጠት ሳይሆን ዘለፋቸውን በሚካሄዱበት ሰዓት እግረ መንገዳችውን ባነሱት የፖለቲካ አተያይ ላይ ሒስ ለማቅረብ ነው፡፡

ይህንንም እንድል ያስገደደኝ እኔ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል ተደውሎ ለቀረበልኝ ጥያቄ በሰጠሁት መልስ ላይ ወይም ባነሳሁት ሐሳብ ላይ ትችት በማቅረብ ፈንታ በእኔ ስብዕና ላይ አሉታዊ በሆነ መልኩ ዘለፋ በመሰንዘራቸው ነው፡፡


ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ የሰጠሁት አስተያያት ዋና ፍሬ ነገር እንደሚከተለው ይነበባል፡፡በሁለተኛ ሹም ሽር የተከናወኑትን የስልጣን መደላደል በምናይበት ጊዜ ህወሓት እንደ ቀድሞው በእጅጉ ተጠናክሮ ብቸኛ የሆነውን ስልጣኑን ተመልሶ ይዟል፡፡ እንግዲህ  እነ  ወ/ሮ ሚሚ ስብሐቱ  በዚህ መሠረታዊ  ሐሳብ ላይ ትችት በመሰንዘር ፋንታ የተሾሙትን ሰዎች ስም እየጠቀሱ ግነት በተሞላበት አኳኋን ማንነታቸውን ማለትም ችሎታቸውን፣ ክህሎታቸውን ፣ ዕውቀታቸውን ሲክቡ በአንፃሩ እኔ ያቀረብኩትን ሐሳብ ሳይተቹ ለአንድ  የዩኒቨርሲቲ  መምህር የማይመጥን (የወረደ) አስተያየት በማለት አልፈውታል፡፡

እሑድ  በሚተላለፈው  ፕሮግራም  ላይ  የሚቀርቡት  ወ/ሮ ሚሚ እና ሌሎች ሁለት ግለሰቦች ቢሆኑም ሁለቱ ሰዎች እንደ ሰው በፕሮግራሙ ላይ የሚያንፀባርቁት የራሳቸው የአስተሳሰብ ልዕልና የሌላቸውና ለሚሚ ልሳን ለማዋስ ወይም  ለማከራየት የተሠማሩ ስለሆነ ይህ ጽሑፍ እነርሱን ሳይሆን በቀጥታ እርሷን የሚመለከት ይሆናል፡፡

ከሁሉ አስቀድሞ ግን ትችቴን ከመጀመሬ በፊት አንድ ነጥብ አንስቼ ማለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ይኸውም እነሚሚ በግለሰብ ደረጃ ለሰነዘሩት ዘለፋ በአደባባይ መልስ መስጠቱ ተገቢ አይደለም፡፡ በመሆኑምእኔ እንዲህ ነኝ፤ እንዲያ ነኝብሎ ስለራስ መናገር ከባሕልም አኳያ ሆነ ከሞራል እይታ አንፃር ተገቢ ሆኖ አናገኘውም፡፡ ሆኖም ግን ሚሚ ካነሳችውዳኛቸውይገባኛልየሚለው ሹመት ስላልተሰጠው ነው፡፡ ኢሕአዴግን የሚተቸውለሚለው ገለፃ ፅብቴን ጥዬ ማለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ከላይ እንደጠቀስኩት ራሴን በመከላከልአይ እኔ ሹመት አልፈልግምየሚል መልስ ለመስጠት ሳይሆን እዚህ በቆየሁባቸው ዓመታት ሹመት የሚፈልግ ሰው ማድረግ የሚገባውን ነገር አጥቼው ወደ ሒስና በመንግስት ላይ ትችት ወደ መሰንዘር የሄድኩበት እንዴት ሊመስላት እንደቻለ መገረሜን ለመግለፅ ያክል ነው፡፡ ምናልባትም በመንግስት ለመሾም፣ለመደጎምና ለመመስገን ያለውን መንገድ በሞኖፖልእኔ ብቻ ነኝ የማውቀውየምትል ከሆነ ስለ እኔ ሹመት ከጃይነት ያለችው እውነት ሊሆን ይችላል፡፡


የሙታን ዲሞክራሲ
 
በገዢው ፓርቲ ልሂቃን አስተሳሰብ አሁን በኢትዮጵያ የተዘረጋው ሥርዓት ወሳኝ የሆኑትን የፖለቲካ ጥያቄዎች ስለፈታ ጊዜው የፖለቲካ ማቀንቀኛናየማብጠልጠልሳይሆን ወደ ልማት የሚተኮርበት ነው፡፡ የዚህ ሐሳብ ዋነኛ ተጋሪ የሆነችው ሚሚ ስብሐቱ ጥያቄ በሚያነሱ ሰዎች ላይ ቁጣዋ የሚነሳው ከዚህ የመነጨ ነው፡፡የነሚሚ ስብሐቱየዚህ ጥያቄ አልቋልየሚለው አስተያየት ጥያቄውን ለማፈንና ለመግደል ከመከጀል የመነጨ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንደሚሉት እነሚሚ ማድረግ የሚፈልጉት ደርግ እንዳደረገው ጠያቂውን ሳይሆን ጥያቄውን እንደ ጥያቄ መግደል መፈለጋቸው ነው፡፡ የዚህ ጽሑፍ ማተኮሪያ በሆነው ፕሮግራሟ ላይም ካነሳቻቸው ነጥቦች አንዱየብሔር ፖለቲካ መልስ ተሰጥቶበት ያበቃ ጉዳይ ነው የሚለው በምሳሌነት መቅረብ ይችላል፡፡

ፖለቲካ አልቋልጥያቄዎች ተፈትተዋልለአገሩቱ የሚበጅ ሐሳቦች ተገኝተዋልአሁን ትኩረታችን ከውይይት፣ ከምክክር እና ከንትርክ ወጥተን ያገኘናቸውን የሚበጁ ሐሳቦች መተግበር ላይ ማድረግ ብቻ ነው የሚያስፈልገውየሚል አካሄድ ነው የተያዘው፡፡ እንዲህ ዓይነቱን አስተሳሰብ አንዳንድ ጸሐፍት ሕይወት አልባ እና የሙታን ዴሞክራሲ ይሉታል፡፡  በአንፃሩ ግን አንድ ማህበረሰብ ዴሞክራሲያዊና ሕያው እንዲሆን የሚከተሉትን ሦስት ንድፈ ሐሳቦች አቅፎ የያዘ መሆን አለበት፡፡ እነርሱም አውጥቶ ማውረድና ምክክር (ደሊበራቲኦን) ፣ ሐሳብን ማብላላት (ረፈለችቲኦን) እንዲሁም የሒስ መንፈስ (ጭሪቲቻል ጽፒሪት) ናቸው፡፡

ይህ እንግዲህ የሚያመለክተን ጉዳይ ማንኛውም ፍልስፍና ወይም የፖለቲካ ሂደት የሚነሱትን የኑሮ ተግባራዊ ችግሮች፣ የሚታዩትን የፖለቲካ መሰናክሎች እንዲሁም የሚደቀኑትን የሞራል ክፍተቶች ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መፍታት ስለማይቻል ከላይ የጠቀስናቸው ሦስት ነጥቦች ለዴሞክራሲያዊ ማሕበረሰብ በጣም አስፈላጊ መሆናቸውን ነው፡፡ እንደሚሚ ስብሐቱ አቀራረብ ግን የኢሐአዲግ የፖለቲካ አካሄድ ብዙ ማሕበረሰባዊ ጥቄዎችን እየፈታ የሚሄድ ስለሆነ እንደገና ወደ ኃላ እየተመለሱ ጥያቄ ማንሳት የአድኃሪ ጠባይ ነው፡፡ በተለይም  አገሪቱ የብሔር ጥያቄን ተሻግራ ካለፈች በኃላ እንደ ዳኛቸው ዓይነቱ ሰዎች ለምን ወደ ኃላ እንደሚመልሱን አናውቅምማለቷ ፖለቲካ ማለቂያ የሌለው የሐሳብ ፍጭት የሚያስተናግድ መድረክ መሆኑን ነው የዘነጋችው፡፡ ለውይይትና ለሐሳብ ፍጭት ደግሞ አቀጣጣዩ ነዳጅ ጥያቄ ነው፡፡ በመሆኑም ውይይት፣ጥያቄ፣ምክክር፣ነቀፊታ፣ትችት ወዘተ። ለአንድ ዴሞክራሲያዊ ማሕበረሰብ ወሳኝና አስፈላጊ ነገሮች ናቸው፡፡
 
አትናገሩአትጠይቁአታንገራግሩአትተቹዝም ብላችሁ ተገዙ የሚለውን የጉልበተኞች ጥሪ ይበልጥ ለማብራራት የ፳ ኛው ክ/ዘመን ታላቅ ደራሲ ከሆነው ፍራንስ ካፍካ ሥራዎች መካከል ትንሽ ትረካ ልጥቀስ፡፡ በአንድ እስር ቤት ውስጥ የሞት ፍርድ ተላልፎባቸው ቅጣቱን የሚጠባበቁ እስረኞች አንድ ቀን ከሰዓት በኃላ አመፅና ረብሻ ጀመሩ፡፡ የከሰዓቱ ፈረቃ የዘብ አለቃ ካመፁት እስረኞች ዘንድ ቀርቦየእናንተ ጓደኞች ከዚህ በፊትም ሆነ ዛሬ ጠዋት እንኳ በነበሩት ረሻኞች ላይ ምንም ዓይነት ረብሻ ሳያነሱ  ተረሽነው ሳለ እናንተ ግን በእኛ ተራ ላይ ረብሻ ማንሳታችሁ ተገቢ ያልሆነና አድልዎን የሚያሳይ ነው፡፡ እንዲያውም ከሞራል አኳያ የሚያስጠይቃችሁን ሥራ እየፈፀማችሁ ነው፡፡ የማታዳሉና ረብሻ ፈላጊ ባትሆኑ ኖሮ እንደዚህ ባለ የብጥበጣ ተግባር ውስጥ ሳትሳተፉ ዝም ብላችሁ ትገደሉ ነበር፡፡ብሎ ወቀሳቸው፡፡

እነ ሚሚም አሁን የሚሉንባለፉት ስርዓታት ዝም ብላችሁ እኛ ስልጣን ስንይዝ በፊት ያላነሳችሁትን የጭቆናና የበደል አቤቱታ አሁን በእኛ ተራ ማንሳታችሁ ተገቢ አይደለም፡፡ ጥሩ ሰዎች ብትሆኑ አርፋችሁ ትገዙ ነበርእንደማለት ነው፡፡


ሚሚ ስብሐቱ ጋዜጠኛ ወይስ ሶፊስት

ጥንታዊው ትልቁ የግሪክ ፈላስፋ ፕሌቶ ዕድሜ ልኩን በሐሳብ ሶፊስቶችን ሲታገል ነው የኖረው፡፡ በመሠረቱ ሶፊስት ማለት በተቀዳሚ አስመሳይ ማለት ነው፡፡ ወይም አስመስሎ የሚያድር ማለት ነው፡፡
በዚህ ዙሪያ ዶ/ር እጓለ ገ/ዮሐንስየከፍተኛ ትምህርት ዘይቤበተባለ መጽሐፋቸውየቀድሞ ዘመን ሶፊስቶች ያቀረቡት የጥቅም አገልጋይ የሆነ አሳሳች ትምህርት በጊዜአችንም ዘመናዊ ዳቦ ለብሶ ወደ እልፍኝ አዳራሽ ለመግባት ይጠይቃል፡፡ ዳቦና ቆዳ ከለየን ግን ቆየንብለዋል፡፡ እኛም ታግለው የመጡትን ፋኖዎችና የከተማፋኖዎችከለየን ቆይተናል፡፡በተጨማሪም እውነተኛ ጋዜጠኞችንና ፕሮፓጋንዲስቶችንም ጠንቅቀን ካወቅንም ውለን ከርመናል፡፡

እንደ እኔ አስተያየት ሚሚ ስብሐቱ በፕሮፓጋንዳ ሥራ ላይ የተሰማራች እመቤት ነች፡፡ ሚሚ ተቀዳሚ ሥራዋ ፕሮፓጋንዳ ነው በምንልበት ጊዜ ምን ማለታችሁ ነው፧ ለዚህ ጥያቄ ቀጥተኛ መልስ ከመስጠታችን በፊት የእርሷ ሬዲዮ በአመለካከትና በአቀራረብ ከመንግስት ሚዲያ ጋር ዝምድና አለው ብለን ስለምናምን ከዛሚ በፊት ትንሽ ስለ ኢትዮጵያ ሬድዮና ቴሌቪዥን ብንናገር ጋሪውን ከፈረሱ ማስቀደም አይሆንብንም፡፡


ሚዲያና አታላዩ ጂኒ

በመሠረቱ የሚዲያው ዋና ሚናና ግብ ሥርዓቱ እራሱን እየወለደ (ረፕሮዱቸ እያደረገ) እንዲሄድና ሕልውናውን ለዘለቄታው ማስጠበቅ ነው፡፡ ለዚህም ተልዕኮው መረጃ ከማቀበል መደበኛ ሥራው ጎን ለጎን የፕሮፓጋንዳ ተግባራትን ያከናውናል፡፡ ለፕሮፓጋንዳ ሥርጭቶቹም ማሳነስ፣ መጨመር፣ ማጋነን፣ ማንኳሰስ፣ መደመር፣ መቀነስ፣ መፍጠር፣ ማንፀባረቅ፣ መወንጀል፣ ማወደስ ዓይነተኛ መሣሪያዎች ናቸው፡፡ እነዚህን የፕሮፓጋንዳ ተግባራት ትንሽ ለማብራራት በአንድ ርዕስ ዙሪያ የተካሄደውን የሁለት ፈረንሳዮች ወግ መጥቀስ ተገቢ መስሎ ይታየኛል፡፡ አንደኛው ፈረንሳዊ ሬኔ ዴካርት የተባለው የ፩፯ኛው ክ/ዘመን ፈላስፋ ነው፡፡ ይህ ፈላስፋ የሰው ልጅ ወደ ትክክለኛው ሐሳብ እንዳይደርስ የሚያደርጉ መሰናክሎች አሉ ይልና ከነኚህ መካከል ባህል፣ወግና የመሪዎች ጫና ተጠቃሾች መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ ይኸውም የሚሆንበት ምክንያት በዋናነት የሰው ልጅ በስሎና ዐውቆ ስለማይወለድ የራሱን የአመለካከት ልዕልና እስከሚያገኝ ድረስ በማሕበረሰቡ ስለሚቀረጽ ውጫዊ የሆኑት የባሕል፣ የወግ የታሪክ ጫናዎች በላዩ ላይ ያርፋሉ፡፡ በመሆኑም በአንድ ማሕበረሰብ ውስጥ ያሉ ግለሰቦች ወደ እውነት እንዲቀርቡ ከተፈለገ በተቀዳሚነት የማሕበረሰቡ አመለካከት መታከምና መጽዳት አለበት ብሎ ያምናል፡፡

በተጨማሪም እንደሬኔ ዴካርት መላምት እንዲያውም ከባህል ውጭ አንድ ሆነ ብሎ አሳሳች የሆነ እርኩስ ሰይጣን ሊኖር ይችላል፡፡ ማኅበረሰቡ ውስጥ ያሉ አሳሳች ነገሮች ዐውቀው ለማሳሳት ሳይሆን ካለማወቅ እና የጠቀሙ እየመሰላቸው የሚያሳስቱ ሲሆን፣ በአንፃሩ የአሳሳቹ ጂኒ ተግባር ግን አስቦና ሆነ ብሎ የሚያደርገው ነው፡፡ ከሬኔ ዴካርት አስተምህሮት የምናገኘው ስሕተት እንደ ስሕተት የግለሰቡ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ከማኅበረሰቡ አመለካከት ጋር የተቆራኘ መሆኑን ነው፡፡ በሌላ በኩል በ፳ኛው ክ/ዘመን መባቻ ላይ የመጣው ፈረንሳው የማሕበረሰብ ጥናት ተመራማሪ ኤሚል ዴርካም፣ ለዴካርትአሳሳች ጂኒ ሊኖር ይችላልለሚል አስተያየት ሲመልስጂኒውም ከጉም ከሰማይ ፣ከወንዝ፣ከተራራ ስር ከምትፈልገው እዚያ የፖለቲካ ማኅበረሰብ ውስጥ ብትፈልገው ታገኘዋለህበማለት ነበር፡፡

ወደ እኛ ጉዳይ በምንመጣበት ጊዜ እኛም አታላዩ ጂኒ እንደ ዴርካይም የፖለቲካ ሥርዓቱ አካባቢ በተለይም በሚዲያ ክፍል ሊገኝ ይችላል ብለን እናምናለን፡፡ ከዚህ አኳያ እህታችን ከተሰማራችበት የፕሮፓጋንዳና የማነሁለል ተግባራት ስንነሳ የሬኔ ዴካርትን ጂኒ ሚና እንደምትጫወት ይሰማናል፡፡ ይህንኑ አሳሳች ጂኒ በመፍራት ማንኛቸውም የዴሞክራሲያዊ አገራት መንግስታት የራሳቸው ሚዲያ እንዳይኖራቸው በሕግ ተከልክሏል፡፡ እንደ ቪኢኤ የመሰሉ የሚዲያ ተቋማት ዜናዎቻቸውን ለውጭ አድማጮችና ተመልካቾች እንጂ ለአገር ውስጥ ታዳሚያን ማሠራጨት የማይችሉት ለዚህ ነው፡፡


ህወሓት እና የትግራይ ሕዝብ

በመሠረቱ ህወሓት ትግርኛ የሚናገሩ ሰዎች የፈጠሩት የፖለቲካ ፓርቲ እንጂ የትግራይ ሕዝብ ማለት አይደለም፡፡ በሌላ በኩል ፓርቲው የተወሰኑ የትግሪኛ ተናጋሪዎች እንጂ የሁሉም የትግራይ ሰዎች ፓርቲ ማለትም አይደለም፡፡ ይህንን ለመለየት በጣም የላቀ ትምህርት አስፈላጊ ሆኖ አናገኘውም፡፡ ሁለቱን መለያየት ካልቻልን እንደ ሚሚ ስብሐቱ ህወሓት ሲነካ ትግራይ ተነካ፤ስለ ህወሓት ሲወራ ስለ ትግራይ ማውራት ተደርጎ መቁጠር ይሆናል፡፡

ለዚህም ማሳያነት እንዲሆን ለጋዜጣው በሰጠሁት አስተያየትስልጣን ተመልሶ ወደ ህወሓት እጅ ገባማለቴንዳኛቸው ስልጣን ወደ ትግራይ ተመለሰ አለብላ አቅርባዋለች፡፡ እዚህ ላይ አፅንዖት ለመስጠት የምፈልገው ያላልኩትን ማለቷ ላይ ብቻ ሳይሆን ፓርቲና ዘርን አንድ አድርጎ የሚያቀርብላት አዕምሯዊ ቀረፃ እንዳላትም ለማሳየት ጭምር ነው፡ ይህንንም ስል የሽተቷ ምንጭ ከአቀራረብ ወይንም ከማወቅ አለማወቅ (ዐፒስተሞሎጊቻል) ሳይሆን ያላት አዕምሯዊ ኑባሬ (ኦንቶሎግይ) ከዘርና ከነገድ ውጭ እንዳታይ እንደሚያደርጋት መግለፄ ነው፡፡ ሽተቷያጋጣሚሳይሆንየተፈጥሮመሆኑን ልብ ይሏል፡፡

እንደዚህ ዓይነት አዕምሯዊ ኩነት የግድ ሚሚ ስብሐቱን ህወሓት ሲነካ ትግራይ ተነካ እንድትል፤ስለ ህወሓት ሲወራ ስለ ትግራይ የተወራ አድርጋ እንድትቆጥር ያደርጋታል፡፡ በዚህ ረገድ ሚሚ ብቸኛ ሳትሆን በዛ ያሉ የአመለካከት ወንድምና እህቶችም እንዳሏት በእርግጠኛነት መናገር ይቻላል፡፡

ከአዕምሯዊ ግንዛቤ ውጭ የፖለቲካ ደጀን ይሆነናል ከማለትም ሆነ ተብሎ የትግራይን ሕዝብመጡባችሁበሚል ፈሊጥ እንደመሸሸጊያ ይጠቀሙበታል፡፡ ከዚህ ጋር ተያያዥ ያለው የተማሪነት ገጠመኜን በምሳሌነት ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡ በአፄ ኃ/ሥላሴ ዘመነ፡ መንግስት የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሳለን ብዙ ጊዜ በፖለቲካ ምክንያት ረብሻ ይነሳ ነበር፡፡ አንድ ቀን ከሰዓት በኃላ የት/ቤቱ አሜሪካዊ ዳሬክተር ሁላችንንም ሰብስበው ተግሳፅና ቁጣ ከሰነዘሩብን በኃላ ከመሐከላችን የነበረውን በጣም የታወቁ የአፄ ኃ/ሥላሴ የቅርብ ዘመድ የራስነት ማዕነግ ያላቸውን ሰው የልጅ ልጅ ከሁላችንም በተለየ ነጥለው የሚከተለውን ተናገሩት፡፡አንተ ብዙ ጊዜ ረብሻ ላይ እፊት ፊት ትቀድማህ ሆኖም ግን ችግር በሚመጣብህ ጊዜ ከዚህ ቀደም ደጋግመህ እንዳደረግኸው አያጥ ጫማ ውስጥ ገብተህ ትደበቃለህ ፡፡

አሁንም እኔ እንደሚታየኝ አንዳንድ የህወሓት አቀንቃኞች ፓርቲው ላይ ለሚሠነዘረው ሒስ መልስ መስጠት ሲቸግራቸውና የአመለካከት አጣብቂኝ ውስጥ ሲወድቁ  ሮጠው የትግራይ ሕዝብጫማውስጥ ይደበቃሉ፡፡ በመሆኑም ለእርሷ ህወሓትን የተቸ ሁሉ ፀረ፡ትግሬና ትምክህተኛ ነው፡፡

በፕሮግራሙ ላይ ከተነሱት ነገሮች በጣም የገረመኝ ሚሚ ስብሐቱ ሳትሆን ከተወያዮቹ አንዱእኔ የምፈራው አሁን እነዚህ ሰዎች (እነ ዳኛቸው) ክቡር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድኃኖምን ትግሬ ብለው እንዳያዋርዷቸው ነው፡፡ሲል መስማቴ ነው፡፡እንዳያዋርዷቸውየሚለው መቼስ የሚገርም ቃል ነው፡፡ እኔ እስከገባኝ ድረስ በዚህ አነጋገር ለማለት የተሞከረው ሦስት ጉዳኞችን ነው፡፡ አንደኛ፡፡ የተሾሙትን ትግሬዎች እንበላቸውበማለት ሹመቱ የት ቦታ እንደሄደ ለማድበስበስ ነው፡፡ ሁለተኛው፡፡ ደግሞ የተሾሙትን ከብሔር በላይ የሆኑ ሰዎች አድርጎ ለማቅረብ ነው፡፡ በሦስተኛ ደረጃ::  ትግርኛ የሚናገርን ሰውኤርትራዊ ነኝእስካላለ ድረስ ትግሬ ነው ብለን ብንገልፀው ሰውየውንማዋረድየት ላይ እንደደሆነ ሊገባኝ አይችልም፡፡


መደምደሚያ

ጤናማ የሆነ የፖለቲካ ውይይት ለማካሔድ ከስድብና ከዘለፋ ባሻገር በአስተያየትና በሐሳብ ላይ የተሞረኮዘ ሙግትና ውይይት ምንጊዜም ለዴሞክራሲ ማበብ ትልቅ አስተዋፅዖ ያደርጋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ከዚህም በተጨማሪ ዴሞክራሲ ተመራጭ የሆነው የሐሳብ ልዩነት የሚያስተናገድበትን መድረክ አመቻችቶ ስለሚያቀርብ ነው፡፡ ሆኖም ከዚህ አኳያ የሚሚ ስብሐቱን የቅርብ የፖለቲካ አካሄድ ስንፈትሽ ለዴሞክራሲ ይበጃሉ ተብለው ከተቀመጡት ወሳኝ መርሆችዎች ያፈነገጠች መሆኗን እንገነዘባለን፡፡

አንደኛ፡፡ የሐሳብ ልዩነትን በኃይልና በዘለፋ ለመወሰን መሞከር ኢ፡ዴሞክራሲያዊ መሆኑን ትዘነጋለች፡፡

ሁለተኛ፡፡ የዴሞክራሲ ግብ ሄዶ ሄዶ ነጻነትን (ሊበርትይ) መጎናፀፍ ነው፡፡ነፃነት ስንል ደግሞ የቡድን ብቻ ሳይሆን የግለሰብም   ነፃነት ማለታችን ነው፡፡እነ ሚሚ እንደሚያደርጉት ከእነርሱ ሐሳብ ውጪ የቀረበን ድምፅ እንዳይሰማ ለማፈን ከመሞከር በተጨማሪየብዙኃን መገናኛ በእጃችን አለበማለት የሐሳብ ብዝኃነትን ገድሎ አንድን ሐሳብ በብቸኝነት ለማንገስ የሚደርግ ሙከራ የነፃነት ገፈፋ ብቻ ሳይሆን ትልቅ የመብት ጥሰት መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ሦስተኛ፡፡ ዴሞክራሲ ከሁሉም በላይ በሥነ፡ምግባር ፣በፖለቲካ እንዲሁም በማህበረሰብ ጉዳይ የተኮተኮተ መልካም ዜጋ ለማፍራት የሚያስችል ሥርዓት ነው፡፡ከዚህም አኳያ ስናየው ዴሞክራሲ ትልቅ ት/ቤት ነው፡፡

ለዚህ የማስተማር ተግባሩ ሬዲዮን ጨምሮ ሎሎች መገናኛ ብዙኃን ዓይነተኛ መሳሪያዎች ናቸው፡፡ሚሚ ስብሐቱ ግን ይህንን መልካም ሚና ሙሉ በሙሉ ለመጫወት የፖለቲካ ድባቡ ባይፈቅድላትም በራሷ ተነሳሽነት ትንሽም እንኳ ጥረት ስታደርግ አይስተዋልም፡፡

እንዲያውም የሚሚን ፕሮግራም በምናይበት ጊዜ የመንግስት ሚዲያ የራሱን ሐሳብ ለማቅረብ የተሳነው ይመስል፤ እርሷም ተጨማሪ የግል ሬዲዮ በብዛት ሳይሆን በጥቂቱ በሌለበት አገር ውስጥ በሞኖፖል ለተያዘው የዜና አውታር አጋር መሆኗ የሚያሳዝን ነው፡፡
ዓለማየሁ ገ/ሕይወትእታለምበተሰኘ ስብስብ ግጥሞችበምድር ማሕፀንበሚለው ግጥሙ በዋናነት የቀይሽብር ሰለባ የሆኑት ሰማዕታት አጽም ተቆፍሮ ሲወጣ በወቅቱ የተሰማውን ስሜት የገለጸ ሲሆን፣ ወደፊትም ይኼ ነገር እንዳይደገም ያሰጠነቀቀበትን ምክር ያካተተ ግጥም ነው፡፡ ዓለማየሁ በግጥሙ በተለይም ስለወደፊቱ ያሰጠነቀቀበት እኔ ካነሳሁት ሐሳብ ጋር ተያያዥነት ስላላው ጥቂት ስንኞችከምድር ማሕፀንተውሼ ለአንባቢያን እጋብዛለሁ፡፡


።አፈር ያደረግነው፤
ጭንጫ መሬት ያልነው
ያገራችን ምድር ፣ተራራው ሜዳችን
ሰርጡ ወጣ ገባው፣ለምለሙ መስካችን
በተማሰ ቁጥር፣ወጣ ታሪካችን፡፡
ሰርዶና ቄጠማ
ሰንበሌጥ አክርማ
  እሚያበቅለው አፈር፣
ዋንዛና ባህርዛፍ፣
ዳጉሳና ነጭ ጤፍ
እሚያፈራው ምድር
ዳግም ተማሰና፣ተገኝ ሌላ እውነት
የአንድ ትውልድ ታሪክ
የአንድ ትውልድ ሃፍረት፦
ሕጻንና አዛውንት
ኮረዳና አሮጊት
ጎልማሳና ወጣት
እንበለ ርህራሄ፣የተጨፈጨፋ የተቀበሩበት፦
ነገ እሚቆፈረው ፣እሚማሰው አፈር
ከህሊና ንቅዘት፣
እንዲሆን የጸዳ፣ከዘመን ቸነፈር
በምንወጥነው ግብር፣በምንተክለው ችግኝ
ተንኮል እንዳይገኝ፣
ህፀፅ እንዳይገኝ፣
ሰርክ ፀሎታችን፣
ነገ እሚነበበው፣ታሪክ ሕይወታችን
የሚያስደስት እንጂ ፣ላይሆን እሚያስከፋ
አንገት እሚያስደፋ፣
ሀገር እሚያለማ፣እንጂ እማያጠፋ
መሆኑን ማሳየት፣አለብን በይፋ፦
ከእንግዲህ ምድራችን፣ማሕፀኗ ሲቃኝ
በወርቅና በአልማዝ፣ ተገጥግጦ እንዲገኝ
ለእውነት እንቁምና፣ቸር ቸረሩን እንመኝ፡፡

No comments:

Post a Comment